Reporter

Reporter


ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በ6 ሳምንታት ውስጥ በአዲስ አበባ የስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት እንደሚጀምር የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አንዋር ሶሳን ዋቢ አድርጎ ሪፖርተር አስነብቧል።


ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በቀናት በፊት በድሬዳዋ ከተማ መጠነ ሰፊ የደንበኞች የኔትዎርክ ሙከራ መጀመሩ ይታወሳል። አገልግሎቱ በራሱ መሰረተ ልማት የተጀመረ መሆኑ ተጠቁሟል።


የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አንዋር ሶሳ ፤ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ሲካሄድ የነበረው የመሠረተ ልማት ስምምነት በቶሎ ባለማጠናቀቁ አገልገሎቱን ለማስጀመር ጊዜ መውሰዱን ገልፀዋል።


በሌላ በኩል ፤ ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ትርፍ ለማግኘት ቢያንስ 5 ዓመታት ሊፈጅበት እንደሚችል አስታውቋል።


በዓለም አቀፍ ደረጃ በነዳጅ፣ በሲሚንቶና በሌሎች ግብዓች ላይ ዋጋ መጨመሩ ኩባንያው በቶሎ ትርፍ ለማግኘት እንቅፋት ሊሆንበት እንደሚችል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አንዋር ሶሳ ተናግረዋል።


የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ባልቻ ሬባ (ኢንጂነር) ለሪፖርተር ጋዜጣ በሠጡት ቃል ፤ ኩባንያው እስከ ሚያዚያ 2015 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ የኢትዮጵያን 25 በመቶ የኅብረተሰብ ክፍል የሚሸፍን አገልግሎት እንዲያቀርብ ውል ገብቷል ብለዋል።


በዚሁ በተጠቀሰው ጊዜ የሚጠበቅበትን ካላሟላ ኦዲት ተደርጎ በገባው ውል መሠረት ቅጣት ይጣልበታል እንደሚጣልበት ፤ ይሁን አንጂ የቴሌኮም ኩባንያው አሁን በተሳካ ሁኔታ ሥራውን እያከናወነ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡


የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፤ ኩባንያቸው የዋጋ ጦርነት ውስጥ የመግባት ፍላጎት እንደሌለው ተናግረዋል። ይሁን እንጂ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ፈጣን የቴሌኮም አገልግሎት እንደሚያቀርብ አስረድተዋል፡፡


ከፍተኛ የሆነ ውድድር እንደሚጠብቃቸው የሚናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው ኩባንያው የሚቀጥራቸው ሠራተኖች ባላቸው ብቃት ለሚቀጠሩባቸው አካባቢዎች ያላቸው ግንዛቤና የቋንቋ ብቃት መሠረት ተደርጎ እንደሆነ ለሪፖርተር ጋዜጣ አስረድተዋል፡፡

በድሬዳዋ ከተማ አገልግሎት በጀመረው የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የሙከራ ኔትወርክ ደንበኞች ዳታ መጠቀም፣ ጥሪዎችና የጽሑፍ መልዕክቶችን ከሳፋሪኮም ኢትዮጵያና ከኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች ጋር መለዋወጥ፣ እንዲሁም ዓለም አቀፍ ጥሪዎችን ማድረግ ያስችላቸዋል።

ሳፋሪኮም ወደ ሳፋሪኮም ሆነ ወደ ኢትዮ ቴሌኮም ሲም ለድምፅ በደቂቃ 50 ሳንቲም የሚያስከፍል ሲሆን ለኢንተርኔት በ10 ብር 120 ሜጋ ባይት፣ 900 ሜጋ ባይት በ50 ብር እንዲሁም ሁለት ጌጋ ባይት በ100 ብር ለ30 ቀናት በመደበኛነት እየሸጠ ነው።

(ሪፖርተር ጋዜጣ)

(የክፍያ ዝርዝር ከአል ዓይን ኒውስ)

@tikvahethiopia

Report Page