BSZGC
DOCH HDየኢፌድሪ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚንስቴር ሚንስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) እና በርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) የተመራ የፌደራል ፣ የክልልና የዞኑ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች የሚዛን አማን ኤርፖርት የግንባታ ሂደትን ጎበኙ።
በጉብኝቱ በሚዛን አማን ኤርፖርት የግንባታ ተቋራጭ ድርጅት ማናጀር በኢንጂነር ኢዮብ ሞላ ማብራሪና ገለጻ ተደርጎላቸዋል።
የሚዛን አማን ኤርፖርት በ2013 ዓመተ ምህረት በጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ የመሰረተ ድንጋይ ተጥሎ ወደ ስራ የተገባ ሲሆን አሁን ላይ የግንባታ ሂደቱ 79 በመቶ መድረሱን ኢንጂነር ኢዮብ ተናግረዋል።
አሁን ላይ 1.1 ኪሎ ሜትር የአስፓልት ስራ ፣ የአጥር ፣ ጊዜያዊ ተርሚናል እና የማቆሚያ ስፍራ ግንባታዎች እየተሰሩ መሆናቸው ተናግረዋል። 2.3 ኪሎ ሜትር የውሀ መስመር የመቀየር ስራ መሰራቱን ገልጸው የወሰን ማስከበር ፣ የዝናብ መብዛትና ተራራማ ቦታዎችን የመቁረጥ ስራ ጊዜ መውሰዱን ገልጸዋል።
የፕሮጀክቱ ስራን እሰከ ታህሳስ 2018 ድረስ አጠናቆ ለማስረከብ እየተሰራ መሆኑን ኢንጂነሩ ጠቁመው ግንባታው ሲጠናቀቅ 2.9 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 45 ሜትር ስፋት ይኖረዋል ብለዋል።
የህዝቡ የልማት ፍላጎትና ቀናነት ታክሎበት ፕሮጀክቱ ዛሬ ላይ ከ79 በመቶ በላይ አፈጻጸም ላይ መድረሱን ገልጸው የፌደራል መንግስት ለቀሪ ክፍያዎች ድጋፍ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ለኤርፖርት ግንባታው የዞኑም ሆነ የክልሉ መንግስት የቅርብ ክትትል ሳይለየው እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ተቋራጭ ድርጅቱም ትልቅ አቅም ያለውና በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ አስፓልት ማንጠፍ ስራ መግባቱ የሚደነቅ ነው ብለዋል።
ለልማት ተነሺዎች የካሳ ክፍያ ዞኑ ትልቅ ዋጋ መክፈሉን ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸው ቀሪ የካሳ ክፍያዎችን ለማጠናቀቅ የፌደራሉ መንግስት ድጋፍና ብድር እንዲያመቻቹም ጠይቀዋል።
የኢፌድሪ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚንስቴር ሚንስትር ዶክተር አለሙ ስሜ እንደተናገሩት ከ2 አመት በፊት ፕሮጀክቱን መጎብኘታቸውን ገልጸው አሁን በጥሩ አፈጻጸም ላይ ይገኛል ብለዋል። ግንባታው አለም አቀፍ ህግን መሰረት አድርጎ እየተገነባ መሆኑን ገልጸው ቀሪ ቴክኒካል ስራዎችን በፍጥነት ማጠናቀቅ እንደሚገባም ገልጸዋል።
ቀሪ ተነሺዎች ፣ የካሳ ክፍያ ጉዳዮችን ከክልሉ መንግስት ጋር በመነጋገር ለመፍታት ይሞከራል ያሉት ሚንስትሩ ከታህሳስ በፊት በሚጠናቀቅበት ሂደት ላይ ተቋራጩ እንዲሰራ አቅጣጫ ሰጥተዋል።
በጉብኝቱ ሚንስትር ዶክተር አለሙ ስሜ ፣ ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ፣ የሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሐንስ አበራን ጨምሮ የፌደራል ፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የቤንች ሸኮ ዞን የመንግሰት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት