#S

#S


ከሐምሌ 11 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በነበሩ ተከታታይ ቀናት በደቡብ ክልል በሲዳማ ዞን በተፈጸሙ ጥቃቶች፣ ከ900 በላይ ሰዎች መፈናቀላቸው ታወቀ፡፡ በጥቃቱ የበርካቶች ሕይወት ማለፉ ቢታወስም፣ ቁጥራቸው ግን እስካሁን በውል አይታወቅም፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፣ ከተፈናቃዮቹ ውስጥ አብዛኞቹ ሴቶችና ሕፃናት ናቸው፡፡

የሲዳማ ተወላጅ ያልሆኑት እነዚህ ተፈናቃዮች በአሁኑ ጊዜ በአብያተ ክርስቲያናት፣ በመስጊዶችና ባስጠለሏቸው ማኅበረሰቦች ቤቶች ውስጥ እንደሚገኙና ዕርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው ተገልጿል፡፡

የመንግሥትና የሰብዓዊ ዕርዳታ አጋሮች የጋራ ቡድን ከሐምሌ 16 ቀን ጀምሮ ባደረገው የመስክ ምልከታ፣ 481 ተፈናቃዮች በኦሮሚያ ክልል በጉጂ ዞን በቦሬ ወረዳ ተመዝግበዋል ተብሏል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 457 ያህሉ በቦሬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን፣ 24 ተፈናቃዮች ደግሞ በቦሬ መስጊድ እንደሚገኙ የማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤቱ አስታውቋል፡፡

በቦሬ ወረዳ ከሚገኙት 481 ተፈናቃዮች ውስጥ 50 ያህሉ ሕፃናት ሲሆኑ፣ 30 የሚሆኑት ደግሞ በዕድሜ የገፋ አዛውንት ናቸው ተብሏል፡፡

ቀሪዎቹ ተፈናቃዮች ያሉባቸው ከጉጂ ዞን ጋር የሚዋሰኑት ሲዳማ ዞን ውስጥ የሚገኙት ኡላ፣ ጮርኔና ቦና ወረዳዎች ደግሞ ለተፈናቃዮች እጅግ ከባድ እንደሆኑ ተገልጿል፡፡

ተፈናቃዮቹ ለቡድኑ በተፈጸመባቸው ጥቃት ምክንያት ንብረታቸውን ከማጣታቸውም በላይ ከቤተሰቦቻቸውም ጋር መለያየታቸውን መናገራቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የጉጂ ዞን የአደጋ ሥጋት አመራር ጽሕፈት ቤት በቆሎ፣ ዘይትና የሕፃናት ምግብ ማቅረቡን፣ የአካባቢው ማኅበረሰቦች ብርድ ልብስና የተለያዩ ምግቦች መለገሳቸው ተጠቁሟል፡፡ ተፈናቃዮቹ ወደ ቀዬአቸው እስከሚመለሱ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ጽሕፈት ቤቱ መግለጹ ተመልክቷል፡፡

ክልል ከመሆን ጥያቄ ጋር በተያያዘ በሲዳማ ዞን ኤጀቶ በመባል የሚታወቀው የወጣቶች ስብስብ ባስነሳው ተቃውሞ ምክንያት፣ ሲዳማ ያልሆኑ ወገኖች ላይ በተፈጸመ ጥቃት በሰው ሕይወትና በንብረት ላይ ከባድ ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡

ከሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ክልሉ በፌዴራል የፀጥታ ኃይሎች ኮማንድ ፖስት ሥር መዋሉም አይዘነጋም፡፡ ሁኔታዎች ተለውጠው ተፈናቃዮች እንደገና እስከሚቋቋሙ ድረስ ምግብ፣ የንፅህና መጠበቂያዎችና የሕክምና ድጋፍ ከማስፈለጉም በተጨማሪ፣ የተጠፋፉ ቤተሰቦችን ማገናኘትም ሌላው ፈታኝ ሥራ እንደሚሆን ተገምቷል፡፡

Via #REPORTER

@tsegabwolde @tikvahethiopia

Report Page