#ETH

#ETH


BBC News የአገልግሎት/ ምርት ምልክት

menu

ኤች አይ ቪ ለምን በምራቅ እንደማይተላለፍ እና ሌሎች የተሳሳቱ አመለካከቶች

  •  29 ኅዳር 2018

ይህንን ለማጋራት በ ኢሜይል

 ይህንን ለማጋራት በ ፌስቡክ

 ይህንን ለማጋራት በ ትዊተር

 ይህንን ለማጋራት በ ዋትስአፕ



እንደ የዓለም ጤና ድርጅት ከሆነ ኤች አይ ቪ በዓለም አቀፍ ደረጃ አሳሳቢ የጤና ጉዳይ ከመሆን ባለፈ እስከ አሁን ድረስ ከ35 ሚሊየን በላይ ሰዎችን ቀጥፏል።

ባለፈው ዓመት ብቻ አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ከኤች አይ ቪ ጋር በተተያዙ መንስኤዎችን ህይወታቸው አልፏል።

37 ሚሊዮን የሚያህሉ ሰዎች ቫይረሱ ያለባቸው ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 70 በመቶ የሚሆኑት አፍሪካ ውስጥ ናቸው። በአውሮፓዊያኑ 2017 ደግሞ 1.8 ሚሊዮን ሰዎች በበሽታው ተጠቅተዋል።

በኤች አይ ቪ ቫይረስ መጋለጥ በኤድስ መያዝን ማወቅያ ብቸኛ መንገድ ነው።

ለመጀመሪያ ጊዜ በሽታው በ1980ዎቹ ከተስፋፋ በኋላ የኤች አይ ቪ ቫይረስ እንዴት እንደሚተላለፍ እና ከኤች አይ ቪ ጋር መኖር ምን እንደሚመስል እጅግ በጣም ብዙ የተሳሳቱ አመለካከቶች፤ ጭፍን ጥላቻ እና መገለልን ፈጥረዋል።

ዓለም አቀፍ የኤድስ ቀን በሚከበርበት ዕለት በጣም በተለመዱት አንዳንድ ግንዛቤዎች ላይ እናነጣጥራለን።

የተሳሳተ አመለካከት: ኤች አይ ቪ ፖ ዘ ቲቭ ከሆኑ ጋር በመሆኔ በኤች አይ ቪ እያዛለሁ

ይህ የተሳሳተ ግንዛቤ ለረዥም ጊዜ በኤች አይ ቪ በሚኖሩ ሰዎች ላይ መድልዎ አስከትሏል።

ከፍተኛ የግንዛቤ ማስጨበጫ ዘመቻዎች ተካሂደውም በአውሮፓዊያኑ 2016 እንግሊዝ ውስጥ 20 በመቶ የሚሆኑት ሰዎች ኤች አይ ቪ በቆዳ ንክኪ ወይም በምራቅ እንደሚተላለፍ ያምኑ ነበር።

ይሁን እንጂ በንክኪ፣ በእንባ፣ በላብ፣ በምራቅ ወይም በሽንት አይተላለፍም።

በእነዚህ ምክንያቶችም በኤች አይ ቪ አይያዙም:-

  • ተመሳሳይ አየር መተንፈስ
  • ማቀፍ፣ መሳም ወይም እጅ መጨባበጥ
  • የመመገቢያ ዕቃዎችን መጋራት
  • የውሃ ፍሳሽ መጋራት
  • የግል ዕቃዎችን መጋራት
  • የስፖርት ማዘውተሪያ መሳሪያዎችን በጋራ መጠቀም
  • የመጸዳጃ ወንበርን፣ የበርን እጀታ ወይም እጀታውን መንካት

በቫይረሱ ከተያዘ ሰው ኤች አይ ቪ የሚተላለፈው እንደ ደም፣ የዘር ፍሬ፣ የሴት ብልት ፈሳሽ እና የጡት ወተት በመሳሰሉ የፈሳሽ ልውውጥ ነው።

የተሳሳተ አመለካከት: መድኃኒቶች ኤች አይ ቪን ሊፈውሱ ይችላሉ

በጭራሽ እውነት አይደለም። ተለዋጭ መድሃኒት፤ ከግብረ ስጋ ግንኙነት በኋላ መታጠብ ወይም ከድንግል ጋር ግብረ ስጋ ግንኙነት መፈጸም ከኤች አይ ቪ ጋር ምንም ግንኙነት የላቸውም።

በሕንድ፣ በታይላንድ እና ከሰሃራ በታች ባሉ የአፍሪካ ሃገራት ከድንግል ጋር ወሲብ መፈጸም ከኤች አይ ቪ ያድናል የሚለው የተሳሳተ አደገኛ አመለካከት አለ።

ይህ አስተሳሰብ ወጣት ልጃገረዶችን አስገድዶ ከመድፈር በተጨማሪ አንዳንዴም ሕፃናት ጭምር እንዲደፈሩ እና በኤች አይ ቪ እንዲያዙ በር ከፍቷል።

ሰዎች ቂጥኝ እና ጨብጥ መያዛቸውን ተከትሎ ይህ ሐሳብ በ16 ኛው ክፍለ ዘመን አውሮፓ ውስጥ ስር ሰዶ ነበር፤ ይህ ግን ለእነዚህ በሽታዎችም አይሠራም።

ጸሎት እና ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓቶች ሰዎች አስቸጋሪ ሁኔታዎችን እንዲቋቋሙ ሊረዱ ቢችሉም በቫይረሱ ​​ላይ ምንም ዓይነት ህክምናዊ ተጽዕኖ የላቸውም።

የተሳሳተ አመለካከት: ትንኞች ኤች አይ ቪን ሊያሰራጩ ይችላሉ

ምንም እንኳን ቫይረሱ በደም ቢተላለፍም፤ በሚነክሱ ወይንም ደም በሚመጡ ትንኞች ምክንያት ቫይረሱ አይተላለፍም። ለዚህ ደግሞ ሁለት ምክንያቶች አሉ፡

1) ከዚያ በፊት የነከሱትን ሰው ደም በሚነክሱበት ወቅት አለማውጣታቸው እና

2) ኤች አይ ቪ በውስጣቸው ለአጭር ጊዜ ብቻ መቆየቱ ነው

ስለዚህ እርስዎ ብዙ ትንኞች እና ከፍተኛ የኤች አይ ቪ ተጋላጭነት ባለባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ቢሆንም ሁለቱ ነገሮች ተዛማጅ አይደሉም።

የተሳሳተ አመለካከት: በአፍ በኩል በ ሚፈጸም ወሲብ ኤች አይ ቪ አልያዝም

በአፍ የሚፈጸም ወሲብ ከሌሎች የወሲብ ዓይነቶች ይልቅ ለአደጋ የማጋለጥ ዕድሉ አነስተኛ መሆኑ እውነት ነው። ከ10,000 ጊዜ የቫይረሱ መተላለፍ ዕድል ከአራት ያነሰ ነው።

ነገር ግን ኤች አይ ቪ ኤድስ ካለባቸው ሰዎች ጋር በአፍ የሚፈጸም የግብረ-ሥጋ ግንኙነት ቫይረሱ ሊከሰት ይችላል። ለዚህ ነው ዶክተሮች በአፍ በኩል ለሚደረግ ግብረ ስጋ ግንኙነትም ቢሆን ኮንዶም መጠቀምን የሚመክሩት።

የተሳሳተ አመለካከት: ኮንዶም ከ ተጠቀምኩ በ ኤች አይ ቪ አልያዝም

በጾታዊ ግንኙነት ወቅት ኮንዶም ቢቀደድ፣ ቢንሸራትት ወይም ፈሳሽ ካስተላለፈ ለኤች አይ ቪ ተጋላጭነትን ሊከላከሉ አይችሉም።

ለዚህም ነው ስኬታማ የኤድስ ዘመቻዎች ኮንዶም በመጠቀም ላይ ብቻ ሳይሆን የኤች አይ ቪ ምርመራ በማድረግ እና ካለባቸውም ህክምናውን ወዲያውኑ በማግኘት ላይ ማተኮርን የሚመክሩት።

የተሳሳተ አመለካከት: ምንም የ ሕመም የለም ማለት ኤች አይ ቪ የለም ማለት ነው

አንድ ግለሰብ ምንም ምልክት ሳይታይበት ከኤች አይ ቪ ጋር አሥር ወይም አሥራ አምስት ዓመት ሊኖር ይችላል። በበሽታው ከተያዙ በኋላ ባሉት የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት እንደኢንፍሉዌንዛ በሽታ ምልክት የሚመስል ትኩሳት፣ ራስ ምታት፣ ማሳከክ ወይም የጉሮሮ ህመም የመሳሰሉ ምልክቶች ሊያጋጥሙ ይችላሉ።

ሌሎች ምልክቶች የበሽታ መከላከያ ስርዓቱ ሲዳከም በጊዜ ሂደት የሚመጡ ናቸው። እነዚህም የክብደት መቀነስ፣ ትኩሳት፣ ተቅማጥ እና ሳል ናቸው።

ሕክምና ካላገኙ ሳንባ ነቀርሳ፣ ክሪፕቶኮካል ማጅራት ገትር፣ በከባድ የባክቴሪያ በሽታ እና እንደሊምፎማስ እና ካፖሲስ ያሉ ካንሰሮችን የመሳሰሉ ከባድ ሕመሞች ሊከሰቱ ይችላሉ።

የተሳሳተ አመለካከት: ኤች አይ ቪ ያላቸው ሰዎች በለጋ ዕድሜያቸው ይሞታሉ

ኤች ቨይ ቪ እንዳለባቸው የሚያውቁና ህክምናውን በትክክል የሚከታተሉ ሰዎች ጤናማ ኑሮ እየመሩ ነው።

እንደ ዩኤንኤድስ ከሆነ ቫይረሱ ካለባቸው ሰዎች 47 በመቶ በሚሆኑት ቫይረሱ እጅግ የተጨፈለቀ ከመሆኑ የተነሳ በደም ውስጥ ያለው የኤች አይ ቪ መጠን በምርመራ "ሊታወቅ" አይችልም።

የተጨፈለቀው ቫይረስ ያለባቸው ሰዎች ከሌለባቸው ሰዎች ጋር ግብረ ስጋ ግንኙነት ቢያደርጉ እንኳን ​​ሊያስተላልፉ አይችሉም።

ይሁን እንጂ ህክምናውን ካቆሙ መጠኑ ከፍ በማለት በሚታወቁበት ደረጃ ላይ ይደርሳል።

የዓለም የጤና ድርጅት እንደገለጸው በኤች አይ ቪ የተያዙ 21.7 ሚሊዮን ሰዎች በአውሮፓዊያኑ 2017 መድኃኒት እየወሰዱ ሲሆን ይህም በ2010 ከነበረው በስምንት ሚሊዮን የሚበልጥ ነው።

ይህ ማለት ቫይረሱ እንዳለባቸው ካወቁ ሰዎች 78 መቶ የሚደርሱት መድኃኒት እያገኙ ነው።

የተሳሳተ አመለካከት: ኤች አይ ቪ ያለባቸው እናቶች ልጆች ሁልጊዜ ተጋላጭ ናቸው

በፍጹም ትክክል አይደለም። ቫይረሱን በቁጥጥር ስር ያደረጉ እናቶች ቫይረሱን ሳያስተላልፉ ልጅ ሊወልዱ ይችላሉ።



Copyright © 2018 ቢቢሲ . ማስተባበያ


Report Page