#ETH

#ETH


የጸጥታ ኃይሉ ጎንደር ላይ በአጠራጣሪ እንቅስቃሴ ላይ አገኘኋቸው ያላቸውን 38 ወጣቶች በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስታወቀ፡፡

ከተያዙት ወጣቶች መካከል አንድ ግለሰብ አራት መታዎቂያዎችን፣ ሌላ አንድ ወጣት ደግሞ 7 የውጭ ሀገር ሲም ካርዶችን እንደያዘ አረጋግጫለሁ ብሏል የከተማ አስተዳድሩ የሰላምና ደኅንነት መምሪያ፡፡

‘ሰሊጥ ለመሰብሰብ ሥራ እየሔድን ነው’ በማለት በጉዞ ላይ የነበሩ ከሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተነሱ 38 ወጣቶች በቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ የተያዙት ትናንት ጥቅምት 10/2012 ከቀኑ 10፡00 ጎንደር ከተማ ቀበሌ 15 ላይ በጸጥታ አካላትና በወጣቶች ትብብር እንደሆነ ታውቋል፡፡

በቁጥጥር ሥር የዋሉትም ወቅቱ የሰሊጥ መሰብሰቢያ ጊዜ ያለፈበት እና ጉዟቸውም አጠራጣሪ በመሆኑ ነው ብሏል የጎንደር ከተማ አስተዳድር የሰላምና ደኅንነት መመሪያ ለአብመድ በሰጠው መረጃ፡፡ የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንደበት ከበደ እንደተናገሩት ወጣቶቹ ለሌላ ተልዕኮ እየሄዱ እንደሆነ በመጠርጠር በ4ኛ ፖሊስ ጣቢያ በቁጥጥር ሥር ሆነው ምርመራ እየተካሄደባቸው ይገኛል፡፡

እስካሁን በተደረገ ምርመራ አንድ ግለሰብ አራት የተለያዩ መታዎቂያዎችን፣ ሌላ አንድ ግለሰብ ደግሞ ሰባት የውጭ ሀገራት የሞባይል ሲም ካርዶችን እንደያዙ መረጋገጡን አቶ አንደበት ገልጸዋል፡፡

ሦስተኛው ተጠርጣሪ ወጣት በአንድ ወር ውስጥ በተደጋጋሚ በሺህዎች የሚቆጠር ብር በባንክ ማንቀሳቀሱን፣ አራተኛው ግለሰብ ደግሞ በሁለት የተለያዩ ስሞች የተዘጋጁ መታዎቂያዎችን ይዞ እንደተገኘ ነው የተገለጸው፡፡ ምርመራው በቀሪዎቹ ተጠርጣሪዎች ላይም እንደቀጠለ ታውቋል፡፡

ምርመራውን አጠናክሮ በመቀጠል ተጠርጣሪዎቹ በትክክል ለምን ዓላማ እየሄዱ እንደነበር እና ከእነማን ጋር ግንኙነት እንዳላቸው በማጣራት ጉዳዩን ለሕዝብ ይፋ እንደሚያደርግ የጎንደር ከተማ አስተዳድር የሰላምና ደኅንነት መመሪያ ለአብመድ አስታውቋል፡፡

Via AMMA

Report Page