#eth

#eth


በአፋር ክልል ከሰሞኑ የተፈጸመው ጥቃት የታቀደና በውጭ ኃይሎች የተደገፈ እንደነበር የክልሉ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ አስታወቀ፡፡

የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አህመድ ሙሐመድ ለአብመድ እንዳስታወቁት ጥቃት አድራሾቹ የተደራጁና የሶማሌ ላንድ የሠሌዳ ቁጥር ያለው ተሽከርካሪ የሚጠቀሙ ነበሩ፡፡ ቅዳሜ ከሌሊቱ 9፡00 እስከ ቀኑ 10፡00 ድረስ አፋንቦ ወረዳ ሰንጋ የሚባል መንደር በተፈጸመው ጥቃት የ17 ሰዎች ሕይወት ማለፉን፣ በርካቶች መቁሰላቸውንና እንስሳትም መዘረፋቸውን ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡

ጥቃት የተፈጸመበት መንደር ከጂቡቲ ድንበር 35 ኪሎ ሜትር አካባቢ ርቀት የሚገኝ መሆኑን ያመለከቱት አቶ አህመድ በጥቃቱ ሕጻናትና ሴቶች ክፉኛ ሰለባ መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡ 

በአንዳንድ የመገናኛ ብዙኃን ጥቃቱ የተፈጠረው በግጦሽና ውኃ ምክንያት በአፋርና ኢሳ ጎሳዎች መካከል የተፈጠረ እያስመሰሉት መሆኑን ያመለከቱት አቶ አህመድ ‹‹ጥቃቱ ፈጽሞ የአፋርና የኢሳ ጎሳዎች አይደለም›› ብለዋል፡፡

በጥቃቱ የተሳተፉት ኃይሎች ‹‹የሶማሌ ላንድ ሰሌዳ ያለው ተሽከርካሪ ተጠቅመዋል፤ የአልሸባብ ወታደሮች የሚለብሱትን የፊት መሸፈኛና ጥቁር አርማም ተጠቅመዋል›› ብለዋል፡፡ ‹‹የአፋር ሕዝብ በሕይወት የመኖር መብቱ ሊረጋገጥለት ይገባል›› ያሉት ኃላፊው ጥቃቱ የመጀመሪያ አለመሆኑንም አመልክተዋል፡፡ ከአራት ወራት በፊት መሰል ጥቃት ተፈጽሞ እስከ አምስት ሰዎች ሕይወት በዚሁ አካባቢ ማለፉንም ነው ያስታወሱት፡፡ ከመጀመሪያው ጥቃት ጋር በተያያዘ ስድስት ተጠርጣሪዎች በሕግ ቁጥጥር ስር ውለው ምርመራው እየተጣራ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ አካባቢው ከዚህ ቀደም የኮንትሮባንድ ንግድ መተላለፊያ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡ 

አካባቢው ኔትወርክ የማይሠራበትና የመሠረተ ልማት እጥረት ያለበት መሆኑ ጥቃቱን በፍጥነት ለመከላከልም ሆነ ቁስለኞችን ለማጓጓዝ አስቸጋሪ እንደነበርም አመልክተዋል፡፡የአካባቢውን ሠላም ለማረጋገጥ የፌዴራሉ መንግሥት ልዩ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባው ያሳሰቡት አቶ አህመድ ‹‹የሀገር መከላከያ ሠራዊት ወደ አካባቢው አልተሠማራም›› ብለዋል፡፡የተፈጸመውን ጥቃት ለማውገዝ በአፋር ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ዛሬ ሰልፎች መካሄዳቸውንም አስታውቀዋል፡፡ አቶ አህመድ እንደተናገሩት አዋሽ አርባ፣ አፋምቦ እና ገዋኔ ላይ ሠልፎች ተካሂደዋል፡፡ የአፋር ሕዝብ ደኅንነት እንዲረጋገጥም ሰልፈኞቹ መጠየቃቸውን አመልክተዋል፡፡

ምንጭ፦ AMMA

@tsegabwolde @tikvahethiopia

Report Page