#ETH

#ETH


ቅዱስ ሲኖዶሱ በዛሬው አስቸኳይ ጉባኤው በሶስት ጉዳዮች ላይ ይወያያል።

በዛሬው ዕለት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በሦሰት ዐበይት ጉዳዮች ጥልቀት ያለው ውይይት አድርጎ የመፍትሄ ውሳኔዎችን እንደሚያሳልፍ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ ለዋዜማ ሬዲዮ ገልጸዋል፡፡

በመጀመሪያ የሚያየው አጀንዳ ሕዝቡንና ቤተ ክርስቲያናን የመጠበቅ ሓላፊነት ስላለበት ቅዱስ ሲኖዶስ የኦሮሚያ ቤተ ክህነትን ጉዳይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ይመለከተዋል ብለዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ እንዳሉት መግለጫውን የሰጡት አካላት ጉዳዩ የማይመለከታቸው ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አይወክልም፡፡ ምክንያቱም መግለጫ ሰጭዎች የራሳቸውን አሳብ ይዘው ነው የተነሡት፡፡ አሳቡ በራሱ የቤተ ክርስቲያኗን መዋቅር የሚጻረር ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ቤተ ክርስቲያን እስከወዲያኛው እንደማትደግፋቸው አበክረው ተናግረዋል፡፡

ሁለተኛው አጀንዳ ቤተ ክርስቲያኗ በቀጣይ ከመንግሥት ጋር እንዴት መቀጠል እንዳለባት ቅዱስ ሲኖዶስ ይወያያል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የቤተ ክርስቲያን ጥያቄዎች መንግሥት በቀጣይ በምን አግባብ መመለስ እንዳለበት እንዲሁም በቤተ ክርስቲያን በኩል ደግሞ መስተካከል ያለባቸው ጉዳዮች ካሉ ቅዱስ ሲኖዶስ እንደሚወያይባቸው ተገልጿል፡፡ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ አያይዘውም መንግሥት በልዩ ልዩ ችግሮች የተወጠረ እንደሆነ ቤተ ክርስቲያን ትረዳለች ብለዋል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ ቅዱስ ሲኖዶስ ይወያይበታል ተብሎ የሚጠበቀው ደግሞ የቅርብ ጊዜውን ጨምሮ በልዩ ልዩ ጊዚያት አብያተ ክርስቲያናት ይቃጠላሉ፣ ምእመናን ይሰደዳሉ፣ ካህናት ይገደላሉ፡፡ እነዚህን ጉዳዮች ቅዱስ ሲኖዶስ በስፋትና በዝረዝር ከተወያየ በኋላ የመፍትሄ አቅጣጫ ያስቀምጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓትን፣ ቋንቋና እውቀትን የሰጠች እናት ብትሆንም ዛሬ ዛሬ ግን በየጊዜው በልዩ ልዩ ቦታዎች የሚኖሩ ምእመናኖቿ በፍርሃት እየኖሩ፣ በየጊዜው የአምልኮ ቦታቸው እየተቃጠለ፣ ምእመናኑ እየተሰደዱ እንዲሁም ሕፃናት ለችግር እየተዳረጉ ይገኛሉ ብለዋል ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ።

#WAZEMARADIO


Report Page