#ETH

#ETH


የአ.አ. ፖሊስ ኮሚሽን በከተማዋ ንፋስ ስልክ ላፍቶ በ2 አባላቱ ለተፈጠረው ድርጊት ኅብረተሰቡን ይቅርታ ጠየቀ

*************************************

በአዲስ አበባ ከተማ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ፣ ጎፋ ማዞሪያ አካባቢ ነሐሴ 20 ቀን 2011 ላይ ‘ሕጋዊ የኮሚሽን ሥራ እንሠራለን’በሚሉ እና ‘እኛም ሰፈራችን ስለሆነ እንሠራለን’ በሚሉ ግለሰቦች መካከል የተፈጠረውን ግጭት ለማብረድ የፖሊስ አባላት የወሰዱት እርምጃ አነጋጋሪ ሆኗል።

በአካባቢው የነበሩት ፖሊሶች ፀብ ውስጥ የነበሩትን ግለሰቦች ‘ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሔዳችሁ ዳኝነት ታገኛላችሁ’ ቢሉም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው አለመግባባት ተፈጥሮ የፖሊስ አባላቱ የተወሰኑ ሰዎችን መደብደባቸውን የአ.አ. ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን የኢንዶክትሪኔሽን እና የሕዝብ ግንኙነት ምክትል ዳይሬክተር ኮማንደር ፋሲካ ፈንታ ለኢቲቪ አራት ማዕዘን ዝግጅት ክፍል አረጋግጠዋል።

ፖሊሶቹም ራሳቸው ደንብ ልብሳቸውን ለብሰው፣ ሥራ ላይ ተሰማርተው እያሉ፣ አንደኛው ላይ ከእነ ልብሱ ፖሊሱን በማነቁ፣ ሌላኛው ላይ ደግሞ መሣሪያ ጭምር ለመቀማት እና የመተናነቅ ድርጊት ተፈጽሞባቸዋል ብለዋል።

በዚህም የተነሣ ፖሊሶቹ ነገሩን ለማብረድ ጥይት ተተኩሰዋል፣ድብደባም ተፈጽሟል በማለት ኮማንደር ፋሲካ ተናግረዋል።

የተፈጠረውን ድርጊት ተከትሎ የፖሊስ አባላቱ ላይ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስፈላጊውን ማጣራት እያደረገ መሆኑንም ገልፀዋል። ሆኖም ለድርጊቱ የአ.አ. ፖሊስ ኮሚሽን ኅብረተሰቡን ይቅርታ ይጠይቃል ብለዋል።

በድርጊቱ ላይ ተሳትፎ የነበራቸው ሁለት ፖሊሶች መታሰራቸውን፣ ጉዳዩን ለማወቅም በአካባቢው ገለልተኛ የሆኑ ሰዎችን የመጠየቅ፣ እውነተኛ ነገሩ መነሻው ምንድነው፣ የሚባለው ነው ወይስ ከዚያ ውጭ ነው የሚለውን ለማጣራት ኮሚሽኑ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑንም ኮሚሽኑ ለኢቲቪ ገልጿል።

ሆኖም ድርጊቱ ውስጥ የተሳተፉት የፖሊስ አባላት አዲስ እንደሆኑ እና ምንም ዓይነት የሥልጠና ጉድለት እንደሌለባቸው ያስታወቀው ኮሚሽኑ ፣ ኅብረተሰቡ የራሱ ልጆች መሆናቸውን በመረዳት፣ እነርሱ በሚሰጡት ዳኝነት ካልረካ ቅርብ ያለው አመራር ላይ ሔዶ ዳኝነት ለመውሰድ ወደ ፖሊስ ጣቢያ መሄድ እንደሚገባም መክሯል።

በመጨረሻም ኅብረተሰቡ ከፖሊስ ጎን ካልቆመ በስተቀር በተወሰነ የፖሊስ ኃይል ብቻ የወንጀል መከላከል ሥራ እንደማይሠራ በመረዳት ጥፋተኛ ፖሊሶቹን በማጋለጥ እና ሕግ ፊት እንዲጠየቁ በማድረግ እንዲሁም ስህተታቸውን ብቻ ሳይሆን ጥሩ ሥራቸውንም በጎላ መልኩ በማቅረብ ሊያበረታታቸው እና ወንጀልን በጋራ መከላከል ላይ ሊሳተፍ እንደሚገባ የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ ኮሚሽን የኢንዶክትሪኔሽን እና የሕዝብ ግንኙነት ምክትል ዳይሬክተር ኮማንደር ፋሲካ ፈንታ ለኢቲቪ ተናግረዋል።

#ETV

Report Page