#BBC

#BBC


'ወዲ ማማ' በሚል የቅጽል ስም የሚታወቀው ኤርትራዊ ሙዚቀኛ፣ ተክለ ነጋሲ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በማይታወቁ ሰዎች ጥቃት እንደተፈጸመበት ተነገረ።

ድምጻዊው ባለፈው እሁድ ከሰዓት በኋላ ገርጂ በሚገኘው አንበሳ ጋራዥ አካባቢ በእግሩ በሚጓዝበት ወቅት ማንነታቸውን በማያውቃቸው አምስት ሰዎች ጥቃቱ እንደተፈጸመበት ተክለ ለቢቢሲ ተናግሯል።

ጨምሮም ጥቃቱን ከፈጸሙበት ሰዎች ጋር ምንም አይነት ንግግር እንዳልነበረና አላማቸው ጉዳት ማድረስ እንደነበረ ገልጿል።

"ምንም አይነት ንግግር አልተናገሩኝም፤ በቀጥታ ወደ ድብደባ ነበር የገቡት" ሲል ተናግሯል።

ድምጻዊው ተክለ ነጋሲ ሱዳን ውስጥ በነበረበት ጊዜ በደረሰበት የመኪና አደጋ እግሩ ተሰብሮ እንደነበር ጠቅሶ፤ እግሩ ላይ ብረት እንዳለውና ጥቃት ያደረሱበት ሰዎች በተደጋጋሚ በአደጋው ጉዳት የደረሰበት እግሩን ይመቱት እንደነበር ተናግሯል።

አጭር የምስል መግለጫ
የተክለ ነጋሲ ሕክምና ማስረጃ

ከዚህም በመነሳት ከባድ አደጋን ለማድረስ ዕቅድ እንደነበራቸውና ጥቃቱ የታቀደና "በደንብ የሚያውቁኝ መሆን አለባቸው" በማለት ግምቱን አስቀምጧል።

ድማጻዊው በደረሰበት ድብደባ ሳቢያ በቀኝ እጁ፣ በአፍንጫው፣ በጭንቅላቱና የግራ ኩላሊቱ ላይ ከባድ ጉዳት እንደደረሰበትም ለቢቢሲ ተናግሯል።

ኤርትራዊው ተክለ የትግርኛና የትግረ ቋንቋዎች ዘፋኝ ነው።

የገርጂ ፖሊስ ጣቢያ ባልደረባ የሆኑት ምክትል ሳጅን ዮሴፍ ተስፋዬ፣ አርቲስቱ በትናንትናው ዕለት ስለደረሰበት አደጋ ሪፖርት እንዳደረገ በመግለጽ "ትናንት በደረሰን መረጃ መሰረት አምስት ሰዎች መሆናቸውና አካላዊ ጥቃት አድርሰው ምንም ነገር ሳይወስዱበት በመሰወራቸው ከዝርፊያ ጋር የሚያያዝ ነው የሚል ግምት የለንም" ብለዋል።

በተጨማሪም "ተጎጂ አለባበሳቸው ወይም መልካቸው ማስታወስ የሚችል ከሆነ ተከታትለን ልንደርስባቸው እንችላለን" ሲል ለቢቢሲ ምክትል ሳጅኑ ተናግረዋል።

(BBC)

Report Page