BBC

BBC


የአውሮፓ ሕብረት ለኤርትራ ሊሰጥ የነበረውን ከ120 ሚሊዮን ዩሮ ድጋፍን ለሌሎች አገራት ለመስጠት ሐሳብ ማቅረቡን ቢቢሲ ዘግቧል።

ሕብረቱ ከኤርትራ ጋር በተለያዩ መስኮች ለማከናወን ያቀዳቸው ተግራት በወቅቱ ለማከናወን ባለመቻሉ የተያዘው ገንዘብ ወደ ሌላ ተግባር እንዲውል ሐሳብ መቅረቡን የአውሮፓ ሕብረት ዓለም አቀፍ ትብብር ገልጿል።

በዚህም የአውሮፓ ሕብረት ለኤርትራ መድቦት የነበረው 121 ሚሊዮን ዩሮ ወደሌሎች አገሮች እንዲዘዋወር ሐሳብ ቀርቧል ብሏል።


ሕብረቱ ከጥቅምት 2018 ጀምሮ የአገሪቱን የፖለቲካ ድባብ ለማሻሻል፣ ለምጣኔ ሀብት እድገትና እና በሰብዓዊ መብት ጥበቃ ማሻሻያዎች ዙርያ ከኤርትራ ጋር የመስራት ውጥን ይዞ ሲሰራ እንደነበር የኮሚሽኑ የዓለም አቀፍ ትብብር ዘርፍ አስታውሷል።

ከዚህ ጎን ለጎን ከኢትዮጵያ ጋር የተፈረመው የሰላም ስምምነት እንዲተገበር፣ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል የምጣኔ ሀብት ትስስር እንዲፈጥሩና አገሪቱ ከድህነት የምትወጣባቸው መንገዶችን ለመቀየስ ታቅዶም ነበር።

የአውሮፓ ሕብረት አባል አገራት ሕብረቱ ከኤርትራ ጋር በጥምረት ሊሠራቸው ካሰባቸው ዘጠኝ ክንውኖች ስምንቱን አጽድቀው፤ 121 ሚሊዮን ዩሮ ተመድቦ ነበር።

ነገር ግን ሚያዝያ 26 የአውሮፓ ሕብረት የአፍሪካ ትረስት ፈንድ (EUTF) የተመደበው ገንዘብ ለሌሎች አገራት እንዲሰጥ ሐሳብ አቅርቧል።

አባል አገራቱ በሐሳቡ ከተስማሙ ገንዘቡ ወደሌሎች አገራት ይዞራል።

ለኤርትራ የተመደበውን ገንዘብ ለሌላ አገር የመስጠት ሐሳብ የተነሳው የትግራይ ጦርንት ከመቀስቀሱ በፊት ቢሆንም፤ የኤርትራ ወታደሮች በጦርነቱ መሳተፋቸው በሚተላለፈው ውሳኔ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር ተገልጿል።

የአውሮፓ ሕብረት የዓለም አቀፍ ትብብር ኮሚሽን ለቢቢሲ እንደገለጸው፤ ለኤርትራ ተመድቦ ከነበረው ድጋፍ መካከል 18 ሚሊዮን ዩሮው ከትግራይ ተሰደው በሱዳን ለተጠለሉ ስደተኞች እንዲውል ሐሳብ ቀርቧል።

ከዚህ በተጨማሪም 63 ሚሊዮን ዩሮ የሱዳንን ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ለመደገፍ፣ በደቡብ ሱዳን የተከሰተውን እና ወደ ረሀብ እየተሸጋገረ ያለውን የምግብ እጥረት ለመቅረፍ 20 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም የምሥራቅ አፍሪካ ተፈናቃዮችና ስደተኞችን ለመደገፍ 20 ሚሊዮን ዩሮ እንዲመደብ ተጠይቋል።

አውሮፓ ሕብረት የአፍሪካ ትረስት ፈንድ ለኤርትራ ሊሰጠው የነበረው ድጋፍ ከኤርትራ መንግሥት ፍቃድ ሳያገኝ የጊዜ ገደቡ በማለፉ ገንዘቡን ለሌላ አገር የመስጠት ሐሳቡ መሰንዘሩን ሕብረቱ አስምሮበታል።

ሆኖም ግን ከኤርትራ መንግሥት ጋር ፖለቲካዊ ውይይት ለመቀጠል ቁርጠኛ መሆኑን አስታውቋል።

ኤርትራ ለዓመታት በሰብአዊ መብት አያያዟ በአውሮፓና በሌሎች ምዕራባውያን አገራት ስትተች የቆየች ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ውስጥ ወታደሮቿን በማስገባቷ ከፍያለ ተቃውሞ ገጥሟታል።

ምንጭ፦ ቢቢሲ

Report Page