#AA

#AA


በአዲስ አበባ የትራንስፖርት መጨናነቅና እጥረት መኖሩ ታክሲዎች በዘፈቀደ እንዲያስከፍሉ ምክንያት ከሆነ ሰንብቷል፡፡ በአብዛኛዎቹ የትራንስፖርት ቦታዎች ላይ የሚታዩ የተለያዩ ችግሮችን ተቋቁመው አገልግሎቱን ለማግኘት የሚጋፉ ሰዎችም ለስርቆት ሲዳረጉ ማየቱ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡

በአገሪቱ የሚታዩ ክፍተቶችን በመጠቀም ዋጋ መጨመርና ኅብረተሰቡን ማማረር የተለመደ ከሆነባቸው ዘርፎች አንዱ ትራንስፖርት ነው፡፡ የትራንስፖርት አገልግሎት ለማግኘት ከሜክሲኮ ዓለም ባንክ ለመሄድ ተሠልፈው ያገኘናቸው አቶ ኬራሚድ ሙራድ፣ በተለያዩ ቦታዎች መሄድ የሚፈልጉ ተሳፋሪዎችን እንግልት በመመልከት፣ መንግሥት ካወጣው ታሪፍ በላይ በመጠየቅ ተሳፋሪውን አማራጭ የሚያሰጡ፣ በኑሮ ውድነት ላይ ሰውን የሚያማርሩ የታክሲ ትራንስፖርት ሰጪዎች መበራከታቸውን ይገልጻሉ፡፡

መንግሥት በየተለያዩ ቦታ የመደባቸው የሥምሪት ሠራተኞችም፣ ከታሪፍ በላይ ሲጠየቅ ምንም እንደማይሉ፣ ይህም ከዚህ በፊት አውቶቡስ ተራ አካባቢ እንዳጋጠማቸው፣ ችግሩም ትልቅ ዕልባት ማግኘት እንዳለበት አስረድተዋል፡፡

አቶ ግርማዬ አሰፋም በትራንስፖርት ሕገወጥ ታሪፍ ጭማሪ ከተማረሩ ተሳፋሪዎች አንዱ ናቸው፡፡ በሠራተኞችና ተማሪዎች መውጫና መግቢያ ሰዓት አብዛኛውን ጊዜ ትራንስፖርት ለማግኘት እንደሚቸገሩና ረዥም ሰዓት ተሰልፈውም መንግሥት ካወጣው ታሪፍ በላይ ክፍያ እንደሚከፍሉ ተናግረዋል፡፡ መንግሥትም ታሪፍን በተመለከተ ጠንከር ያለ ዕርምጃ በመውሰድ የበኩሉን መወጣት አለበት ሲሉም አክለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ትራንስፖርት ባለሥልጣን የሕዝብ ትራንስፖርት ሥምሪት ቁጥጥር ዳይሬክተር አቶ ቢንያም ኃይሉ፣ በአዲስ አበባ በትራንስፖርት ዙሪያ ብዙ ሕገወጥ ተግባራት የሚፈጽሙ መሆኑን፣ ከእነዚህ ተግባራት አንዱ መንግሥት ካስቀመጠው ታሪፍ በላይ ተሳፋሪውን ማስከፈል እንደሚገኝበት አስረድተዋል፡፡

ይህን መቆጣጠር የሚያስችል የቅጣት አፈጻጸም መመርያ እንዳለና በአሁን ሰዓትም ተግባራዊ እየሆነ እንደሚገኝ የገለጹት አቶ ቢኒያም፣ መንግሥት ካስቀመጠው ታሪፍ በላይ አንድ አሽከርካሪ ለተሳፋሪዎች ሲያስከፍል ከተያዘ በወጣው ሕግ መሠረት የአንድ ሺሕ ብር ቅጣት እንደሚቀጣ አስታውሰዋል፡፡ ተሳፋሪን የማጉላላት፣ ታፔላ ሳይሰቅሉ መንቀሳቀስ፣ መንገዶችን ማቆራረጥም የተለያዩ ቅጣቶች እንደሚያስጥል ተናግረዋል፡፡

አቶ ቢኒያም የተቀመጡ የቅጣት እርከኖችን ጠቅሰው ከታሪፍ በላይ የሚያስከፍሉ ታክሲዎች ከሜክሲኮ አደባባይ ዘነበ ወርቅ አየር ጤና አሥር ብር፣ ከቦሌ ኤድናሞል ሜክሲኮ አሥር ብር እየጠሩ ሲጭኑ የሚናገራቸው አለመኖሩ ተሳፋሪዎችን ምርጫ ያሳጣ የዕለት ተዕለት ገጠመኝ ነው፡፡

አብዛኛውን ጊዜ ከታሪፍ በላይ የሚያስከፍሉ ተሽከርካሪዎችም ከመናኸርያ ወደ መናኸርያ የሚንቀሳቀሱ እንደሆኑ፣ ለምሳሌ ከላምበረት ወደ አውቶብስ ተራ፣ ከቃሊቲ ወደ አውቶብስ ተራ ያሉት እንደሆነ፣ መንግሥት ካወጣው ታሪፍ በላይ በማስከፈል የሚታወቁ ተሽከርካሪዎች አዲስ አበባ ዙሪያ ላይ እንደሚበዙ አክለዋል፡፡

በከተማው እንብርት የሆኑ ቦታዎች ላይ የትራንስፖርት ፍሰቱ ከፍተኛ ችግር ያለበት ቢሆንም፣ አብዛኛውን ጊዜ መንግሥት ካወጣው ታሪፍ በላይ እንደማያስከፍሉ ተናግረዋል፡፡

ሰው ይበዛል ተብሎ በሚታሰቡ ቦታዎች ምሽት ላይ ትራንስፖርት አይገኝም በሚል ታሪፍ ከማይፈቅድላቸው በላይ ማኅበረሰቡን በማስተጓጎል በሚሠሩ መሥመሮች ሠራተኞችን በመመደብ እስከ አራት ሰዓት እንደሚያሠሩ አቶ ቢንያም ገልጸዋል፡፡

የትራንስፖርት ቢሮው የተለያዩ ጥናቶችን በማድረግ የነዳጅ ጭማሪና ሌሎች የመኪና ዕቃዎች ጭማሪ በሚደረግበት ጊዜ የታሪፍ ለውጥ እንደሚያደርግ አክለዋል፡፡

አብዛኛውን ጊዜም መንገዶች ስለሚዘጋጉና ይህም ለተሳፋሪውም ሆነ ለአሽከርካሪው አመቺ ስላልሆነ፤ ኅብረተሰቡ ይህን ችግር በመረዳት የተለያዩ ተሽከርካሪዎችን በመጠቀም ፍሰቱን ለመቀነስ ሀይገር፣ ፐብሊክ ሰርቪስና አውቶብስ እንዲጠቀም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በቀጣይነትም የትራንስፖርት መጨናነቅ እንዳይኖር የአንበሳ ከተማ አውቶብስና የሸገር ኤስክፕረስ ተጨማሪ ተሽከርካሪዎችን ለመግዛት በዕቅድ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ እነዚህ መኪናዎችም ኅብረተሰቡን ከትራንስፖርት እጥረት ለመታደግ እንደሚጠቅሙ አስረድተዋል፡፡

በአዲስ አበባ 352 የሚሆኑ የትራንስፖርት መሥመሮች እንደሚገኙ፣ ከእነዚህ መካከል አምስት ዋና ዋና መነሻ መሥመሮች መገናኛ፣ ጦር ኃይሎች፣ አየር ጤና፣ ስታዲየምና ፒያሳ እንደሆኑ አቶ ቢንያም አስረድተዋል፡፡

በከተማው የሚገኙ ሀይገሮችና ታክሲዎች የታሪፍ ልዩነት ያላቸው ሲሆን፣ የታክሲዎች ትልቁ የታሪፍ የገንዘብ መጠን 18 ብር እንደሆነና የሀይገር ደግሞ ስምንት ብር ከሃያ አምስት ሳንቲም መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የሁለቱም መኪኖች ታሪፍ በ2.5 ኪሎ ሜትር ርቀት መሃል የአንድ ብር ከሃምሳ ሳንቲም ጭማሪ እንደሚኖረው አክለዋል፡፡

Via ሪፖርተር/በተመስገን ተጋፋው/

@tsegabwolde @tikvahethiopia


Report Page