*/

*/

Source

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በሶማሌ እና በአፋር ክልሎች መካከል የተፈጠረው ግጭት በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ ሲል ለሁለቱም ክልሎች ግልፅ ደብዳቤ ጻፈ።

አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ ታህሳስ 22 ቀን 2013 ዓ.ም

አዲስ አበባ ሸዋ

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት መኢአድ ከሰሞኑ በሶማሌ እና በአፋር ክልሎች መካከል የተፈጠረውን ግጭት በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ ሲል ዛሬ ታህሳስ 22 ቀን 2013 ዓ.ም ለሁለቱም ክልሎች በጻፈው ግልፅ ደብዳቤ ጠይቋል።

ሰሞኑን በአፋር እና በሶማሌ ክልል መስተዳድሮች አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ በተፈጠረው ግጭት በወገኖቻችን ላይ በደረሰው የአካል ጉዳት አና የሕይወት መጥፋት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እየገለፅን ለተጎጂ ቤተሰቦች እና ለሁለቱም ማህበረሰብ መፅናናትን እንመኛለን ብሏል የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ለሁለቱም የክልል መንግስታት በጻፈው ደብዳቤ።

ሁለቱ ብሔረሰቦች ተስማምተው፣ተዋደው፣በባህል፣በኃይማኖት እና በኢትዮጵያዊ አንድነት ተጋምደው የኖሩ እንደመሆናቸው መጠን ሁለቱም መስተዳድሮች በሰጧቸው መግለጫዎች ላይ የሕዝባችንን አንድነት እና አብሮነት የሚንድ እና የሀገሪቱን አንድነት የሚፈታተን ሆኖ አግኝተነዋል ነው ያለው፡፡

መኢአድ በደብዳቤው በመሆኑም ዜጎችን ወደ ከፋ ግጭት የሚያመራ እንዳይሆን ያሳደረበትን ስጋት በመግለፅ ሁለቱም መስተዳድሮች እያራመዱት ካለው ውጥረት አንጋሽ የቃላት ጦርነት ወጥተው የገጠማቸውን ተግዳሮት በውይይት ነቅሰው እንዲያወጡ ሲል አጥብቆ ጠይቋል።

የገጠማቸውን አለመግባባትም ወደጎን በመተው በውይይት እንዲፈቱት የጠየቀው መኢአድ በባህል፣ በኃይማኖት እንዲሁም በወንድማማችነት ትስስር አብሮ ለኖረው ሕዝብ ቅድሚያ እንዲሰጡ አሳስቧል።

ሁለቱም ክልሎች ለሰላም ቅድሚያ ሰጥተው የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ጥሪ ያቀረበው የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ኢትዮጵያዊ አንድነትን እንዲያጠናክሩ ሲል ነው በፍፁም ኢትዮጵያዊነት ስሜት መጠየቁን የገለፀው፡፡

የግጭቱ በሰላማዊ መንገድ አለመፈታት የሚጠቅመው ለሕዝባችን ሳይሆን
የኢትዮጵያን መፍረስና የሕዝባችንን ሠላም ማጣት ለሚናፍቁ የውጭ ባላንጣዎች እና ለውስጥ ባንዳዎች ስለመሆኑም ድርጅቱ በደብዳቤው ጠቅሷል።

መኢአድ በጻፈው ግልፅ ደብዳቤ በተለይም የሁለቱ መስተዳድሮች ጥንካሬ እና ሀገር ወዳድነት የሚያበሳጫቸው የጥፋት ኃይሎች እንዳሉ ተገንዝበው ችግሩን በሰለጠነ መንገድ በፍፁም ወንድማማችነት ለማስተካከል ጠንክረው
እንዲሰሩ ነው የአደራ መልዕክቱን ያስተላለፈው፡፡

በመጨረሻም የሁለቱ ወንድማማቾች ግጭት ከፍተኛ ስጋት ውስጥ የከተተው መሆኑን ያሳወቀው መኢአድ እንዲህ አይነት ችግሮች ሲከሰቱ በሁለቱም የየክልል አመራሮች በሰከነ መንገድ ተፈቶ ቀጠናው ወደነበረበት የተረጋጋ የሰላም ኑሮ እንዲመለስና ሰላም እንዲረጋገጥ ሲል ነው የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ያለውን ፅኑ ፍላጎት በመግለፅ ያሳሰበው።

Report Page